Sunday, April 24, 2011

‹እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ ... :፡›

                                             እንኳን  ለብርሃነ ትንስኤ በሰላም በጤና  አደረሳቹ


‹‹እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ ... :፡›› መዝ.፸፯፥፷፭
በዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ
‹‹እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ
የወይን ስካር እንደተወው እንደ ኃያልም ሰው፤ ጠላቶቹንም በኋላው ገደለ ፤ የዘላለም ኀሣር ሰጣቸው፡፡›› መዝ.፸፯፥፷፭
 
 እስራኤላውያን  አምላካቸው እግዚአብሔር ፈርኦንን ከነሠራዊቱ በባሕረ ኤርትራ አስጥሞ ከባርነት ነጻ ካወጣቸው በኋላ ፣ በምድረ በዳ እንደበጎች እየመራ ርስቱን በገመድ ካካፈላቸው በኋላ ያደረገውን ረስተው አሳዘኑት፡፡ ‹‹አስቆጡት ምስክሩንም አልጠበቁም ፤ እንደ አባቶቻቸውም ከዱ ፤ እንደ ጠማማ ቀስትም ተገለበጡ ፣ በኮረብታ መስገጃዎቻቸውም አስቆጡት ፣ በተቀረጹ ምስሎቻቸውም አስቀኑት፡፡
እግዚአብሔርም ይህን ሰምቶ ተቆጣ እስራኤልን እጅግ ናቀ ፤ የሴሎምን ማደሪያ ተዋት›› /መዝ. ፸፯፥፶፯/ በሕዝቡም ላይ ተቆጥቶ በጠላት እጅ እንዲወድቁ አደረገ፡፡ በዚህ ቁጣ የተነሣ ርስቱን ቸል አላቸው ፣ ጎልማሶቻቸውን እሳት በላቸው ካህናቶቻቸው በሰይፍ ሲወድቁ ያለቀሰ የለም፡፡ ለቅሶ በሁሉም ቤት ነበርና አጽናኝ ለመሆን የሚችል ማንም አልነበረም፡፡ ከዚህ በኋላ ግን ለፍጥረቱ የሚራራ አምላክ በምርኮ የወደቁትን ሕዝቡን አሰበ፡፡ ‹‹እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ ፤ የወይንም ስካር እንደተወው እንደ ኃያልም ሰው ፤ ጠላቶቹንም በኋላው መታ  ፤ የዘላለም ኀሣር ሰጣቸው፡፡›› 


መድኃኔዓለም ክርስቶስ እግዚአብሔር ነው!
 ከሦስቱ አካል አንዱ ወልድ እግዚአብሔር ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ እግዚአብሔር የሚለው ስም በተናጠልም በአንድነትም ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ይነገራል፡፡ ሐዋርያዊው ቅዱስ አትናቴዎስ ‹‹አንሰ ሶበ እቤ እግዚአብሔር እብል በእንተ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ›› ‹‹እግዚአብሔር ባልሁ ጊዜ ስለ አብ ስለ ወልድ ስለ መንፈስ ቅዱስ እላለሁ›› ብሏል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስም ‹‹ቃልም እግዚአብሔር ነበረ›› ፤ ‹‹አምላክ በእልልታ እግዚአብሔር በመለከት ድምጽ ዐረገ›› በሚሉትና በሌሎችም ጥቅሶች ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሔር እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታ እንደሆነ በአፍህ ብትመሰክር እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳስነሣው በልብህ ብታምን…›› የሚለው የመጽሐፍ ቃል ሲተረጎም ‹‹እግዚአብሔርነቱ / እግዚአብሔር መሆኑ ፣ መለኮትነቱ ከሙታን እንዳስነሣው›› ተብሎ ነው፡፡ (ሮሜ ፲፥፱) ስለዚህ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመጥራት እግዚአብሔር ብሎ መጥራት በኦርቶዶክሳውያን ዘንድ የተለመደና የታወቀ ነገር ነው፡፡ ‹እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ› በሚለውም ኃይለ ቃል ላይ ወልደ አብ ወልደ ማርያም ክርስቶስ ‹‹እግዚአብሔር» ተብሎ ተጠርቷል፡፡
ትንሣኤ ከእንቅልፍ እንደ መነሣት
በዚህ የቅዱስ ዳዊት ትንቢት የጌታችን ሞት በእንቅልፍ የተመሰለ ሲሆን ትንሣኤው ደግሞ ከእንቅልፍ በመንቃት ተመስሎአል፡፡ በእርግጥም ሞት በመጽሐፍ ቅዱስ በእንቅልፍ ይመሰላል፡፡ ራሱ ጌታችን አልዓዛር በሞተ ጊዜ ‹‹ወዳጃችን አልዓዛር ተኝቶአል ከእንቅልፉ ላስነሣው እሔዳለሁ አላቸው፡፡ እንግዲህ ደቀመዛሙርቱ ፡- ጌታ ሆይ ተኝቶስ እንደ ሆነ ይድናል አሉት፡፡ ኢየሱስስ ስለ ሞቱ ተናግሮ ነበር ፤ እነርሱ ግን ስለ እንቅልፍ መተኛት እንደተናገረ መሰላቸው፡፡ እንግዲህ ያን ጊዜ ኢየሱስ በግልጥ አልዓዛር ሞተ… አላቸው፡፡›› ዮሐ. ፲፩፥፲፫ ቅዱስ ጳውሎስም ስለሞቱ ሰዎች ለመናገር ሲል ‹‹አንቀላፍተው ስላሉቱ…›› ብሏል:: በመጽሐፍ ቅዱስ በብዙ ቦታዎች አንድን ሰው ሞተ ከማለት ይልቅ ‹‹አንቀላፋ›› የሚለው አገላለጽ የተለመደ ነው፡፡ በዚህ አነጋገር ሲሞቱ አንቀላፉ ተብሎ የተጻፈላቸው ነገሥታትና መሳፍንት በብሉይ ኪዳን ከሠላሳ በላይ ናቸው፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ቅዱስ ሉቃስ   የሊቀ ዲያቆናት እስጢፋኖስን ሞት ሲዘግብ ‹‹ተንበርክኮም። ጌታ ሆይ፥ ይህን ኃጢአት አትቍጠርባቸው ብሎ በታላቅ ድምፅ ጮኸ። ይህንም ብሎ አንቀላፋ።›› ሲል ገልጾታል፡፡ (ሐዋ. ፯፥፷)
    እንቅልፍ ከሰው ልጅ ቁጥጥር ውጪ የሆነ ሒደት ነው፡፡ ሰው መተኛትም አለመተኛትም በእርሱ ቁጥጥር አይደለም፡፡ መተኛት ፈልገው እንቅልፍ አጥተው የሚሰቃዩ ሰዎች እንዳሉ ሁሉ እንቅልፍ በዝቶባቸው በፈለጉት ጊዜ ለመነሣት የሚቸገሩም አሉ፡፡ የሚያስተኛም የሚያነቃም እግዚአብሔር ነው፡፡ ለሚሻው እስከ ስድሳ ስድስት ዓመታት እንቅልፍ ሲሰጥ አይተናል በተቃራኒው እንቅልፍ በአይናቸው እንዳይዞር ያደረጋቸውም አሉ፡፡ ‹‹እኔ ተኛሁ አንቀላፋሁም እግዚአብሔርም ደግፎኛልና ነቃሁ››እንዲል፡፡መዝ. ፫፥፭  እንዲሁም ሞት በእግዚአብሔር ሥልጣን ያለ ነው፡፡ ሰው ተኝቶ ሳይነሣ እንደማይቀር በእንቅልፍ የተመሰለው ሞትም ትንሣኤ ያለበት ነው፡፡ ተኝተን እንደማንቀር ሞተንም አንቀርም፡፡
የጌታችን ሞት ደግሞ ከሰው ልጆች ሁሉ ሞት በላይ እንደሰመመን እንቅልፍ የሚቆጠር ነው፡፡ ምክንያቱም ጌታችን በሥጋ ቢሞትም በመለኮቱ ግን ንቁህ ነው፡፡ ‹‹እኔ ተኝቻለሁ ልቤ ግን ነቅቷል›› እንዲል መጽሐፍ (መኃ.፭፥፪) ጌታችን በሥጋው ሲሞት በመለኮቱ ግን ሕያው ነበር፡፡ ለዚህም ነው በዕለተ አርብ በበዓለ ስቅለት ‹‹ኦ ዘጥዕመ ሞተ በሥጋ›› ‹‹በስጋ ሞትን የቀመስከው ሆይ!›› እያልን የምንሰግደው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹በሥጋ ሞተ በመንፈስ ግን ሕያው ሆነ›› ሲል ተናግሯል፡፡ (፩ጴጥ. ፫፥፲፰)
    የጌታችን ሞቱ በእንቅልፍ እንደሚመሰል በምሥጢር የሚያስረዳን ምሳሌም ከኦሪትም እንጥቀስ፡፡ እግዚአብሔር በአዳም ላይ እንቅልፍን ጣለበት በዚህ ሰዓት አዳም ማዕከለ ነቂህ ወነዊም /በመንቃትና በመተኛት መሃል ነበር/ ፤ በዚህ እንቅልፍ ላይ ሳለ ከጎኑ ሔዋንን ፈጠረ ፤ ሔዋን ማለት የሕያዋን ሁሉ እናት ማለት ነው፡፡ ጌታችንም በዕለተ አርብ በመስቀል ላይ በሥጋ ሞቶ በመለኮቱ ግን ሕያው ሆኖ እያለ ጎኑን ሲወጋ  ከጎኑ በፈሰሰው ደምና ውኃ የሕያዋን ሁሉ እናት የሆነች ጥምቀት ተገኝታለች፡፡ ጌታችን ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ የሚለውም ኃይለ ቃል በሥጋው ከሞተው ሞት በሥልጣኑ አፈፍ ብሎ እንደተነሣ በምሳሌ የሚያስረዳ ነው፡፡
ትንሣኤ ስካር እንደመተው
ሌላው በቅዱስ ዳዊት ቃለ ትንቢት የሚገኘው ሃሳብ ትንሣኤ የወይን ስካር እንደመተው ተመስሎአል፡፡ ስለዚህ ሁለተኛው ሞትን እንደስካር የመመሰሉ ቁም ነገር ነው፡፡ በእርግጥ ስካር ለጌታችን የሚነገር ነገር አይደለም፡፡
ስካርን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ‹‹የፈቃድ ዕብደት›› ብሎ ይጠራዋል፡፡ ስካር ታላቁን ጻድቅ ኖኅን እንኳን ያዋረደ ነበር፡፡ ይህ ጻድቅ ሰው ያለ ልማዱ ጥቂት ወይን ቢጠጣ ከአናቱ ላይ ወጥቶ ራሱን አስጣለው፡፡ ዕርቃኑንም ሆነ ፤ ለደፋር ልጁ ለካም መሳቂያና መሳለቂያም ሆነ፡፡ ይሁንና ታማኝ ልጆቹ ሴምና ያፌት የአባታችንን ዕርቃን አናይም ብለው ሸፈኑት፡፡ (ዘፍ. ፱፥፳፩) ታዲያ እንዲህ ዕርቃን የሚያስጥለው ስካር እንዴት ለእግዚአብሔር ይነገራል፡፡ ‹‹የወይን ስካር እንደተወው›› ማለትስ ምን ማለት ነው?
በእርግጥም በጌታችን ሕይወት ስካር ታይቷል ፤ ነገር ግን ስካሩ በመጠጥ ሳይሆን በፍቅረ እጓለ እመሕያው  (በሰው ልጆች ፍቅር ነው)፡፡ ኖህ ሰክሮ ዕርቃኑን እንደሆነ ጌታችን በሰው ልጆች ፍቅር ሰክሮ ዕርቃኑን ተሰቅሏል፡፡ በኖህ ላይ ልጁ ካም እንዳፌዘበት አይሁድ በጌታችን ላይ ዘብተዋል፡፡ ሴምና ያፌት የአባታችንን ዕርቃን አናይም ብለው ዐይናቸውን ጨፍነው የኋሊት እየሔዱ በነጠላ እንደሸፈኑት ጌታችን ዕርቃኑን በተሰቀለበት ዕለት ፀሐይ የጨለመችው ጨረቃ ደም የመሰለችው ፣ ከዋክብትም የረገፉት ብርሃንን ያለበሳቸውን አምላክ ዕርቃኑን ላለማየት ነበር ‹‹ከመ ኢይርአዩ ዕርቃኖ ለዘአልበሶሙ ብርሃነ፤ ብርሃን ያለበሳቸውን ዕርቃኑን ሆኖ እንዳያዩ›› እንዲል፡፡
ጠላቶቹንም በኋላው ገደለ  ፤ የዘላለም ኀሣር ሰጣቸው፡፡
ጌታችን ጠላቶቹን በኋላው መታ ሲባል ከኋላው በተተከለ በመስቀሉ ጠላቶቹ የሆኑት አጋንንትን ድል መንሳቱን የሚያስረዳ ነው፡፡ ስለ ዲያቢሎስ ሲናገርም መጽሐፍ እንዲህ ይላል፡- ‹‹እርሱንም በመስቀል ጠርቆ ከመንገድ አስወግዶታል።›› (ቆላ. ፪፥፲፬) ለዘላለምም ለሠራዊተ አጋንንት በመስቀሉ መሰቃየትን ፣ መስቀሉን ሲያዩ መደንገጥና መሳቀቅን ሰጥቷቸዋል፡፡ ይህንን ያደረገ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር ስሙ ይክበር ይመስገን!
መልካም የትንሣኤ በዓል!! 
የብጹዕ አባታችን  ቃለ ምዕዳን




Friday, April 22, 2011

ሕማሙ ለእግዚእነ (በቅዱስ ኤፍሬም)

                                 ሕማሙ ለእግዚእነ (በቅዱስ ኤፍሬም)
                                                                                                                                                                           
             ይህን እጅግ የሚያስፈራውን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የሕማሙን ታሪክ ለመናገር፣  በከንፈሬም ለመንካት እጅግ እፈራሁ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነም ይህ የሕማሙን ታሪክን መተረክ የሚያሸብር ነው፡፡
Awede Pilatos.jpg
በዛሬው ዕለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኃጥአን ተላልፎ ተሰጠ፡፡ ስለምን ምክንያት ነበር ቅዱስ የሆነው አምላክ እርሱ ያለኃጢአቱ  ለፍርድ ተላልፎ የተሰጠው? አንድም ኃጢአት ሳይሠራ ጌታችን ዛሬ በኃጥአን እጅ  ፍርድን ሊቀበል ተላልፎ ተሰጠ፡፡

ኑ ቅረቡ ስለምን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ  ክርስቶስ ፍርድን ሊቀበል ተላልፎ እንደተሰጠ እንመርምር፡፡ ስለእኛ አዎን ስለበደለኞች ጌታችን ተላልፎ ተሰጠ፡፡ በዚህ የማይደነቅ ማን ነው? ለእርሱስ ክብርን የማይሰጠው ማን ነው ?ባሮቹ በመበደላቸው ጌታቸው ስለእነርሱ ተላልፎ ተሰጠ፡፡ የገሃነምና የጨለማ ልጆች በጨለማ በቅጽበት ሊያጠፋቸው ኃይሉ ያለውን  ፀሐይን ሊይዙት ወጡ፡፡
pic4.JPG
ነገር ግን ጌታችን የእነርሱን አንገተ ደንዳናነት ያውቃል፡፡ በእርሱ ላይ የነበራቸውን ጥላቻ ይረዳል ፡፡ ቢሆንም በራሱ ሥልጣን ለበደለኞቹ በትሕትና ራሱን  አሳልፎ ሰጠ፡፡

ስለዚህም የተናቁ ሰዎች እጅግ ንጹሕ የሆነውን ጌታ ሊያስሩት በቁ፡፡ ከመካከላቸውም አንዱ ማንንም እጅግ ጽኑ በሆነና በማይበጠስ ሰንሰለት የሚያስረው ላይና እኛንም ከእስራታችን የፈታ ጌታ ላይ ተሳለቀበት፡፡

ለራሳቸው ሊሆን የሚገባውን በወይን እርሻቸው ላይ የበቀለውን እሾኽ  ጎንጉነው አክሊል አድርገው በራሱ ላይ አኖሩ፡፡ በተሳልቆም “ንጉሥ ሆይ” ብለውpic3.JPG  ዘበቱበት፡፡

ሕግን የማያውቁ ብሩህና ንጹሕ በሆነው ፊቱ ላይ ምራቃቸውን ተፉበት ፡፡ስለዘህም በእብሪት የፈጸሙትን ተመልክተው በሰማያት ያሉ ሥልጣናትና የመላእክት አለቆች በፍርሃት ተንቀጠቀጡ፡፡

ጌታን ባሮች ሲሰድቡትና ሲያመናጭቁት፤ ሲያፌዙበት፣ ምራቃቸውን ሲተፉበት፣ በጥፊም ሲመቱት የታገሠውን መታገሥ ሳሰላስል እነሆ ልቡናዬ ለሁለተኛ ጊዜ ሲታወክብኝ፣ እንባንም  ሲያፈስ ተመልከቱ፡፡

tekrote res.pngእጅግ ጥልቅ የሆነውን፣ ስለእኛ ያለውን ርኅሩኁ፣ ታጋሽና መሐሪ የሆነውን ተወዳጅ ጌታችንን በደንብ አስተውሉ፡፡ በደስታ መፍሰሻ ገነት ታማኝ አገልጋይ ባሪያ ነበረው፡፡ በበደለ ጊዜ ለቅጣት ተላልፎ ተሰጠ፡፡ ነገር ግን ጌታው የባሪያውን ደካማ የሆነችውን ነፍሱን ተመልክቶ ፤ ለባሪያው ራራለት ምሕረትም አደረገለት፡፡ ስለዚህም ባሪያው በእርሱ ላይ ይሳለቅበት ዘንድ ራሱን አሳልፎ ሰጠ፡፡ሕሊናዬ እጅግ ከመደነቁ የተነሣ ዝም ማለትን ተመኘሁ፡፡ ነገር ግን በዝምታዬ የመድኀኒታችንን ድንቅ ጸጋ ከመናገር መከልከልን ፈራሁ፡፡ እነሆ ስለእኛ የተቀበለውን ሕማም ሳስበው አጥንቶቼ ተነዋወጹብኝ፡፡ ዓለማትን የፈጠረ እርሱ ጌታችን በዛሬው ቀን ፍርድን ይቀበል ዘንድ ከቀያፋ ፊት ቆመ፡፡ ልክ እንደወንጀለኛ ከባሮቹ አንዱ ጌታችንን በጥፊ ጸፋው፡፡ ይህንን ልቡናዬ ባሰበው ጊዜ በፍርሃት ይርዳል፡፡ ባሪያው ተቀምጦአል፡፡ ነገር ግን የእርሱ ጌታ ግን ቆሞአል፡፡ በኃጢአት የተዳደፈው አንዱ አንድም ኃጢአት በሌለበት ላይ ፍርድን ሊያስተላልፍ ተቀምጦአል፡፡
tearekote Libs.jpg
ሰማያትም ተሸበሩ፤ የምድርም መሠረቶች ተነዋወጡ፣ መላእክትና ሊቃነ መላእክት በሽብር ተሞሉ፣ ገብርኤልና ሚካኤል ፊታቸውን በክንፎቻቸው ሸፈኑ፡፡ ባሪያው የጌታውን ፊት በጥፊ ሲጸፋው ሲመለከቱ ዙፋኑን የሚሸከሙት ኪሩቤል በመንኮራኩራቸው ሥር ተሸሸጉ ሱራፌልም በመገረም ክንፎቻቸውን እርስ በእርሳቸው አጣፉ፡፡ ጌታቸው ጽኑ ስቃይን ሲያደርሱበት ሲመለከቱ የምድር መሠረቶችም እንዴት የመሬት መንቀጥቀጥን ይቋቋሙ?አስተዋልኹኝ እናም ተሸበርኹ እንደገናም በእጅጉ ተገረምኹ፡፡ ፍቅር የተባለውን የጌታዬን መከራ አስተውዬዋለሁና፡፡ ይህን በምናገርበት ጊዜ ውስጣዊው አካሌ እንዴት እንደሚነዋወጥብኝ ትመለከታላችሁን? ምክንያቱም በቸርነቱ ሰዋዊ ባሕርያችንን የፈጠረውን በጥፊ መታው፡፡
ወንድሞች እንፍራ እንጂ ዝም ብለን አንስማ፡፡ እነዚህን ሁሉ ጸዋትኦ መከራዎችteqesfo zeban.jpg ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለእኛ መዳን ሲል የተቀበላቸው ናቸውና፡፡
     አንተ ኃጢአት የተሞላህ ባሪያ ሆይ ስለምን ምክንያት ጌታህን በጥፊ እንደመታኸው ንገረን፡፡ ባሮች ከሚጠፉት ጌቶቻቸው ዘንድ ነጻ ለመውጣት ሲሉ በክርስቶስ ላይ መከራን አጸኑበት፡፡ ነገር ግን እናንተ ጎስቋሎች ሆይ ያለአግባብ ጭካኔ በተሞላበት መልኩ ሁሉን ነጻ የሚያወጣችሁን ገደላችሁት፡፡እናንተ ስለፈጸማችሁት ጭካኔ ከቀያፋ ዘንድ አንዳች ብድራትን ጠብቃችሁ ይሆን? በእውኑ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማያውያን ላይ የሠለጠነ ጌታ እንደሆነ አልተማራችሁምን? እናንተ የሁሉ ፈጣሪ የሆነውን ጌታ ለሞት አሳልፋችሁ ሰጣችሁት፤ በዚህም ለዘለዓለም የባሮች ባሪያ ሆናችሁ ትቀራላችሁ፡፡ ከጸጋው ርቃችሁና ተዋርዳችሁ ለዘለዓለም እሳት ተላልፋችሁ ትሰጣላችሁ፡፡
                           ወንድሞች ሆይ እጅግ የሚደንቀውን፣ የንጉሣችን የክርስቶስን ትሕትና  ተመልከቱ! በባሪያው በጥፊ ተመታ፣ እርሱ ግን በትሕትናና በአክብሮት ስለምን እንደመታው በእርጋታ ጠየቀው፡፡
የባሪያውን ቁጣ ጌታው ታገሠ፡፡ ባሪያው ትዝእርተኛ ነበር፤ ጌታው ግን የዋህ ነበር፡፡ በተቆጣ ሰዓት የሚያውከውንና በእርሱ ላይ የሚታበየውን የሚታገሠው ሰው ማን ነው? ጌታ ሆይ የአንተንስ ፍጹም የሆነ ትዕግሥት በቃላት ሊገልጸው የሚችለው ሰው ማን ነው? በእርሱ በጌታችን በኢየሱስ ክርሰቶስ የተወደዳችሁና የምትናፈቁ ኑ በማፍቀርና እርሱን በመናፈቅ ሆናችሁ ወደዚህ ቅረቡ፡፡ ኑ በዳዊት ከተማ ዛሬ ምን እየተፈጸመ እንደነበር ተማሩ፡፡
seqelwo dibe etse.jpg
የሚወደዱና የተመረጡ የአብርሃም ልጆች በዛሬው ዕለት በጌታችን ላይ ምን እየፈጸሙ ነው?  በዛሬው ዕለት ከበደል ንጹሕ የሆነውን ጌታ ለሞት አሳልፈው ሰጡ፡፡ በበደለኞች እጅ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ያለበደሉ በእጨንት ላይ ሰቀሉት፡፡ ኑ የእርሱን መከራ በማሰብ ሰውነታችንን በእንባ እንጠበው፡፡ ምክንያቱም በደለኞች የክብርን ንጉሥ ጌታን ለሞት አሳልፈው ሰጥተውታልና፡፡
                   አንድ ሰው የሚወደውን የእውነተኛ ወዳጁን ሞት ድንገት ቢሰማ በዐይኖቹም ፊት የወዳጁን አስከሬን ቢመለከት ፊቱ በሃዘን ይደምናል፡፡ የፊቱም ብርሃን ይጠቁራል፡፡ እንዲሁ ሰማያውያን፥ አረመኔዎች በመስቀል ላይ ጌታችንን በጭካኔ ሰቅለውት ሲመለከቱ፥ ብሩህ ገጽታቸው ጠፋ፤ ብርሃንን መስጠት ከለከሉ የጌታቸውን ስቃይ መመልከት አልፈቀዱም ራሳቸውን የሃዘን ማቅ አለበሱ፡፡ እንዲሁ ከአብ የሚሰርጸው መንፈስ ቅዱስ የተወደደ የእግዚአብሔር አብ ልጅን መከራ ሲመለከት የቤተ መቅደስን መጋረጃ ለሁለት ሰነጠቀው፡፡ ቤተመቅደሱን ያስጌጡት ጌጦች ድንገት በርግብ አምሳል ተለይተው ወጡ፡፡ የሰማያት ንጉሥ መከራን ከባሮቹ ሲቀበል ተመልክተው ፍጥረታት ሁሉ በፍርሃትና በሽብር ተሞሉ፡፡ ስለመተላለፋችን የተቀበለውን መከራ ማናናቅና በእርሱ ላይም መሳለቅ አይገባንም ፡፡
እኛ ግን ስለእኛ የተቀበለውን መከራና ስቃይ ሰምተን እንስቃለን ራሳችንንም በምድራዊ ደስታ ደስ እናሰኛለን፡፡ ነገር ግን በሰማይ ያለችው ፀሐይ የጌታዋን መከራ ተመልክታ ብርሃኗን በጽልመት ቀየረችው፡፡ ይህን እኛ በተመለከትን ጊዜ አርዓያዋን መከተል አይገባንምን? የሁሉ ጌታ የሆነ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ስለአንተ ተጨነቀ ተሰቃየ፡፡ አንተ የተዋረድክና የተናቅህ ሰው ግን ጌጠኛ በሆኑ ልብሶች ራስህን ታስጌጣለህ፡፡የጌታህን መከራ በምትሰማበት ጊዜ ልብህ አይደነግጥምን? ሕሊናህስ አይነዋወጥብህምን? ብቻውን ንጹሕ የሆነ እርሱ ስለአንተ መተላለፍ ለውርደት ሞት ራሱን አሳልፎ ሰጠ ፡፡ አንተ ግን ይህን እንደማይጠቅም ተራ ነገር ቆጠርኸው ፡፡
pic2.JPG                    አእምሮ ያለው የክርስቶስ መንጋ ሁሉ ይህ በእረኛው ላይ የተፈጸመውን በማስተዋል ይመልከት፡፡ ማንም የራሱን ጥቅም አይመልከት፤ ለራሱም አክብሮትን አይሻ፤ ምክንያቱም ፍጹምና ንጹሕ የሆነው እርሱ ስለእኛ ሲል ነውና ይህን ጽኑ መከራ የተቀበለው፡፡ በሚጠፉ ጌጠኛ ልብሶች ራሱን ማንም አያስጊጥ ከንቱ በሆነ ደስታና ምድራዊ መብልና መጠጥ ራሱን ደስ አያሰኝ፡፡ ነገር ግን በትኅርምትና በእውነተኛ አክብሮት ሆኖ ለፈጠረው ጌታ ራሱን ያስገዛ ፡፡
             አይሁድን የምንመስላቸው አንሁን፡፡ እነርሱ በክፋታቸው የደነደኑ ባለመታዘዛቸው የጸኑ ናቸውና፡፡ እነርሱ የእግዚአብሔርን ጸጋ እና በረከት ባለመቀበል የተቃወሙ ናቸው፡፡ኃያሉ አምላክ ለአብርሃም ስለገባው ቃል ኪዳን ሲል ወደ እነርሱ በረድኤት ቢቀርብም አልተቀበሉትም፡፡ ከሰማያዊ መናን ይመገቡ ዘንድ ሰጣቸው፡፡ ነገር ግን እቢ አሉ፡፡ የምግብን ጣዕም የሚያበላሸውን የግብጽን ሽንኩርት ተመኙ፡፡ በምድረ በዳ ከድንጋይ ውሃ አፍልቆ አጠጣቸው፤ ነገር ግን እንዲህ ያደረገላቸውን ጌታ በመስቀል ላይ ቸንክረውሆምጣጣ ወይንንአስጎነጩት፡፡ወንድሞችሆይ ፈጣሪያቸውንና ጌታቸውን ለሰቀሉት አይሁድ ደቀመዛሙርት እንዳንሆን እንጠንቀቅ ፡፡ የጌታችንን ሕማምና መከራ በማሰብ እግዚአብሔርን በመፍራት እንመላለስ፡፡ ሁልጊዜ ሕማሙን በሕሊናችን እንሳለው፡፡ ምክንያቱም በመስቀል ላይ መዋሉ ስለእኛ መዳን ሲል ነውና፡፡ ስለእኛ ድህነት በመስቀል ላይ ተቸነከረ፡፡ መከራ የማይስማማው ኃጢአትም ያልተገኘበት ጌታ ስለእኛ ሲል የመስቀል ሞትን ሞተ፡፡
                       ወንድሞች ሆይ ለዚህ ውለታው ምንን እንመልስለታለን? ለምንፈጽማቸው ተግባራት ሁሉ ጠንቃቆች እንሁን፡፡ እርሱ ስለ እኛ የተቀበለውን መከራ በክፉ ሥራችን አናስነቅፈው፡፡ ውድ በሆነ ደሙ ንጹሕና ቅዱስ ለሆነው ጌታ የተገዛችሁ አናንት የቤተክርስቲያን ልጆች ሆይ ወደዚህ ቅረቡ፡፡ ኑ በእንባ በመሆን የእርሱን ስቃይና ሕማም በሕሊናችን እናሰላስለው፡፡ በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ በመሆንም እናስበው፡፡ ለራሳችንም እንዲህ እንበል፡- “ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ስለእኛ በኃጢአት ስለጎሰቆልነው ስትል መራራ ሞትን ተቀበልኽ፡፡”
              ወንድሞች ሆይ የምትሰሙት ምን እንደሆነ በጥንቃቄ አስተውሉ፡፡ ኃጢአት የሌለበት የኃያሉ የእግዚአብሔር አብ አንድያ ልጅ ስለኃጢአታችን ለሞት ተላልፎ ተሰጠ፡፡ ልቡናችሁን ክፈቱ፡፡ ስለእኛ መተላለፍ ሲል ስለተቀበለውም መከራ በጥልቀት ተማሩ፤ አስከትላችሁም ለራሳችሁ እንዲህ በሉ፡-
                  “እርሱ የእግዚአብሔር በግ የሆነው ክርስቶስ ፣
                   ፈጣሪያችን በዛሬው እለት ለሞት ተላልፎ ተሰጠ ፣
                    በዛሬዋ እለት አይሁድ ተሳለቁበት ፣
                   በዛሬዋ ቀን አይሁድ ሰደቡት፣
                   በዛሬዋ እለት  ስለእኛ ሲል ፊቱን በጥፊ ተጸፋ፣
                   በዛሬዋ ቀን  በእርሱ ላይ ዘበቱበት፣
                   በዛሬዋ እለት አይሁድ በራሱ ላይ የሾኽ አክሊል ደፉበት ፣
                  በዛሬዋ እለት ስለእኛ በመስቀል ላይ ቸንክረው ሰቀሉት፡፡”
                  ልባችሁ በፍርሃት ይራድ፡፡ ነፍሳችሁም ይህን በማሰብ ትሸበር፡፡ ሁሌም የጌታችሁን መከራና ሕማማት በማሰብ እንባችሁን አፍስሱ፡፡ሁል ጊዜ የክርስቶስ ሕማሙን የምታስቡ ከሆናችሁ፡፡ እንባችሁ በእግዚአብሔር ዘንድ ጣፋጭ መዓዛ እንዳለው መሥዋዕት ይሆንላችኋል፡፡ ነፍሳችሁም እንደ እንቁ ታበራለች፡፡ ሕማሙን ሁል ጊዜ አስቡ፡፡ ሁል ጊዜም እንባችሁ ይፍሰስ፡፡ ስለእኛ መዳን ሲል የተቀበለውን መከራ በማሰብ ሁል ጊዜ እርሱን አመስግኑት፡፡ መከራ መቀበሉ ስለእኛ ጥቅም ነውና፡፡
           እንዲህ ሆነን በተገኘን ጊዜ ዓለምን ሊያሳልፍ ሲገለጥ እንባችሁ በክብሩ ዙፋን ፊት ትምክታችሁ ይሆንላችኋል፡፡ ፍቅር የሆነውን የጌታንን መከራ በማሰብ ጽኑ፡፡ የእርሱን መከራ በማሰብ ፈተናዎችን ሁሉ በጽናት ተወጡአቸው፡፡ ከነፍሳችሁ ለጌታ ምስጋናን አቅርቡ ፡፡ በዐይኖቹ ፊት ሰማያዊውን ጌታንና ስቅለቱን ሁል ጊዜ የሚያኖርና የሥጋ ሥራዎች በመስቀሉ ላይ የቸነከራቸው እርሱ ብፁዕ ሰው ነው፡፡ እርሱ ጌታውን መስሎታል፡፡ይህን መተግበር እግዚአብሔርን የሚያፈቅሩ ባሮች ዓላማና ግብ ነው፡፡ እነርሱም በመልካም ሥራዎቻቸው ጌታቸውን ይመስሉ ዘንድ የሚተጉ ናቸው፡፡
        ንጹሕና ቅዱስ የሆነው ጌታ በመስቀል ላይ ተቸንክሮ እያያችሁ እናንተ በምድራዊ ደስታና ፈንጠዝያ ሕይወታችሁን ማሳለፍን ትወዳላችሁን?  እናንተ ወራዶች ሆይ በመስቀል ላይ የዋለው ጌታ ለአመጻችሁ ብድራታቸሁን እንዲመልስባችሁ አታውቁምን? አናንተ ጌታችን ስለተቀበላቸው መከራዎች ስትሰሙ እንደ ተራ ነገር ትቆጥራላችሁ ትሳለቁማላችሁ፤ በሚያልፈው ምድራዊ ደስታም ሐሴትን ታደርጋላችሁ፡፡ የሚያስፈራው ሰዓት ይመጣል፡፡ በዛን ሰዓት ያለማቋረጥ ታለቅሳላችሁ፤ ስለሕመማችሁም ጽናት በእሳት ውስጥ ሆናችሁ አብዝታችሁ ትጮኸላችሁ፤ ለጩኸታችሁም መልስ የሚሰጣችሁ ወገን የለም፡፡ ለነፍሳችሁም ምሕረትን ብትናፍቁም አታገኙም፡፡
              ጌታ ሆይ ለአንተ እገዛለሁ፡፡ ቸር ለሆንከው ለአንተም ምስጋናን ዘወትር አቀርባለሁ ፡፡ ብቻህን ቅዱስ ወደሆንከውም አንጋጥጣለሁ፡፡ የሰውን ልጅ ሁሉ በምታፈቅረው በአንተ ፊትም በመገዛት እንበረከካለሁ፡፡ አንተንም  አከብርሃለሁ፡፡ ምክንያቱም የአብ አንድያ ልጁ የሆንኸው፣ የፍጥረት ሁሉ ገዢ፣ ኃጢአት የሌለብህ፣ ስለእኔ ስለተናቅሁት ኃጢአተኛ ሰው ስትል፣ ኃጥአን ነፍሳት ከኃጢአት እስራት ነጻ ይወጡ ዘንድ ራስህን ለመስቀል ሞት አሳልፈህ ሰጥሃልና፡፡  ስለዚህ ድንቅ የሆነው ቸርነትህ ጌታሆይ ምን ልክፈልህ!
                             የሰው ልጆችን ለምታፈቅረው ለአንተ ክብር ይሁን፣
                             ርኅሩኅ ጌታ ሆይ ለአንተ ክብር ይገባል፣
                             ስለእኛ መዳን ራስህን ለሞት አሳልፈህ ሰጥተሃልና ለአንተ ክብር ይሆን፣
                             መተላለፋችን ይቅር ላልከው ጌታ ሆይ ለአንተ ምስጋና ይገባል ፡፡
        እኛን ለማዳን ስትል ከሰማየ ሰማያት በመውረድ ወደዚህ ዓለም ለመጣኸው ክብር ይሁን ፡፡
             ከቅድስት ንጽሕት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ በመንሳት እኛን መስለህ ለተገለጥኸው ለአንተ ውዳሴና አምልኮት ይጋባል፡፡ትንሣኤያችንን ለአወጅክልን ንጉሣችን፣ በአንተ እንድንታመን ላበቃኸን፣ ወደ ላይ ወደ አባትህ ላረግኸው፣ በታላቅ ክብር በአባትህ ቀኝ በዙፋንህ ላይ ለተቀመጥኸው ለአንተ ክብር ምስጋና ይሁን፡፡በአባትህ ክብር ከቅዱሳን መላእክቶችህ ጋር ዓለምን ለማሳለፍ በአስፈሪ ግርማ ለምትገለጠው፣ የአንተን ቅዱስ የሆነውን ሕማም ባቃለሉት ላይም ልትፈርድ ለምትመጣው ለአንተ ክብር ምስጋና ይሁን፡፡በዚያን ጊዜ በሰማያት ያሉ ሥልጣናት፣ መላእክትና ሊቃነ መላእክት፣ኪሩቤልና ሱራፌል ፣ በአንድነት  በታላቅ ማስደንገጥና ግርማ ስለአንተ ክብር ይገለጣሉ፡፡
               የምድር መሠረቶች ሁሉ ይነዋወጣሉ፣ እስትንፋስ በአፍንጫው ያለው ሁሉ ከጌታ ግርማና ማስደንገጥ የተነሣ ይርዳል ይንቀጠቀጣል ፡፡በዚያን ጊዜ እጆችህ በክንፎቻቸው ይጋርዱኛል ፡፡ ነፍሴንም ከሚያስፈራው እሳት ይጋርዱዋታል ፡፡ ከጥርስ ማፏጨት ከጽኑ ጨለማ ና ከማያቋርጥ ወዮታ እጆችህ ይታደጉኛል ፡፡እኔም አንተን በማመስገን እንዲህ ማለት እጀምራለሁ “እኛን ኃጢአተኞችን በብዙ የትሕትና ሥራዎችህ በፍቅር ልታድነን ለወደደኸው ለአንተ ክብር ምስጋና ውዳሴና አምልኮ ይሁን” በማለት አመሰግሃለሁ፡፡
                                                                                                                        ለዘለዓለሙ አሜን !!
             http://www.eotc-mkidusan.org/site/                              ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ                                               

Thursday, April 21, 2011

< ሁሉን የያዘው ያዙት ሁሉን የሚገዛውንአሰሩት


 
  <  ሁሉን የያዘውን  ያዙት ሁሉን የሚገዛውን  አሰሩት የሕያውን የአምላክ  ልጅ አሰሩት በቁጣ ጉተቱት በፍቅር  ተከተላቸው ።> 
  የቅዱስ  ዩሐንስ አፈወርቅ  ቅዳሴ


እጸበተ እግር

                  እጸበተ እግር
 በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
             እስራኤል ከግብጽ ባርነት የወጡበትን በዓለ ፍስሐ ወይም  በዓለ ፋሲካ በዓለ መጸለት እያሉ በየዓመቱ  እርሾ የሌለው ቂጣ ጋግረው  በጉን አርደው በመብላት ያከብሩት ነበር ።ዘጸ 11፥32-52 መምህረ ትህትና ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ  ፈጻሜ ህግ ነው እና ይህን በዓል ያከብር ነበር ከእነዚህም  ዕለታት አንዱ ደቀ መዛሙርቱን ይዞ  ያከበረው  በዓል ሲሆን በዚህ ዕለትም ብዙ አስደናቂ  ተአምራትን ከመፈጸሙም በላይ መስዋዕተ ኦሪትን አሳልፎ መስዋዕተ ሐዲስን  የመሰረተበት ቀን ነው ።
        ደቀ መዛሙርቱም ቀርበው  መምህር ሆይ የፋሲካን እራት የት እናዘጋጅልህ ዘንድ  ትወዳለህ ብለው  ጠየቁት እርሱም እንዲህ አላቸው <ከፊታቹ ወዳለ ሀገር ሂዱ የውሃ ማድጋ የተሸከመ ሰው ታገኛላችሁ ከገባባት ተከትላችሁ መምህር ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ፋሲካውን የምበላበት አዳራሽ ወዴት ነው ብሎሃል በሉት ብሎ ዮሐንስ እና ጴጥሮስን ላካቸው >እነርእሱም እንደታዘዙት  ስምዖን ዘለምጽ አግኝትው ነገሩት እርም ደስ እያለው ለሚስቱ ነገግሯት  የተባለውን ያደርግ ዘንድ እደደ 
          ሐሙስ ዘጠኝ ሰዓት ሲሆን ደቀ መዛሙርቱን አስከትሎ ሄደ ከደርቡ ላይ ግምጃ አንጥፈውለት ያን  እየረገጠ ገብቷል መሰሪ ይሁዳ ወደኃላ ቀርቶ ነበር እና ሰለምን ቢሉ በደብረዘይት ከእናንተ አንዱ አሳልፎ ይሰጠኛል ለዚያም ሰው ባይወለድ  ይሻለው ነበር ባላቸው ጊዜ ደቀ መዛሙርቱም ማን ነው የሚክድህ ንገረን ብለው በጠየቁት ጊዜ ጌታም ከከራድዮስ ድንጋይ አንዱን እኔን አሳልፎ የሚሰጠኝ ማን ነው ብሎት በይሁዳ ረስ ላይ ሦስት ጊዜ ዞሮ ንጹሕ  ደም የምታፈስ  ይሁዳ ወዮልህ ብሎ መስክሮበት ይህ መሰሪይ ብሎ ብሎ ድንጋይ ያስመሰከርብኝ ጀምር ብሎ በምን ያገኘኝ  ብሎ ወደ ቤተመቅደስ ሄዶ ከአይሁድ ጋር ይማከር ነበርእና ስለዚህ ነው መጠጥቶ ሊገባ ሲል እለስክንደሮስ የተባለው ጠባቂ ጌታችን ከደቀመዛሙርቱ ጋር ሲገባ አይቶ ብሩህ ማዕጠንት  ይዞ ገባ አንተ ግን በደም የተሞላ ጽዋ ይዘሃል ከአንገትህ እባብ ተጠምጥሞ ለስምህ ምላሱን ያወለበልባል የያዝከው ደም ቢጥብበት ጌታዪ ስለሚያዝንብኝ ቆየኝ ብሎ ምንጸፉን ካነሳ በኃላ አስገብቶታል ።
         ከዚህ በኃላ ከማዕድ ተነስቶ ወገቡን በዝናር ታጥቆ የደቀመዛሙርቱን እግር ሲያጥብ ውኃ በኩስኩስት ይዞ ቀረበ ርዕሰ ሐዋርየሰት ነው እና ከጴጥሮስ ይጀምራል እግርህን አምጣ ልጠብህ አለው ።አቤቱ አንተ እግሬን ታጥበኛለህ? አለው የማደርገው ን ኃላ እንጂ አሁን አታውቀውም አለው ።መቼም ቢሆን እግሬን አታጥበኝም አለ ጌታም ካለጠብኩ ከእኔ ጋር
እድል ፈንታ ጽዋ ተርታ የለህም አለው ።እንዲእህስ  ከሆነ እጄንም እግሬንም ጨምረህ እጠበኝ አለው። ጌታም ፈጽሞ የታጠበ ከእግሩ ሌላ አያሻውም አለ ። እናንተ ንጹሐን ናችሁ ነገርግን ሁላቹም አይደላችሁም አለ ። አጥቦ ሲጨርስ እኔ መምህራችሁና ጌታቹ ስሆን እግራችሁን ካጠብኃችሁ አርእዬን ሰጥቻችኃለሁናእናንተም  የወንድማችሁን እግር ታጥቡ ዘንድ ይገባል ።ነገር ግን ከእናንተ አንዱ ለሞት አሳልፎ ይሰጠኛል አለ ።ማን ይሆን ?   እሆንን አሉ  ኅብስት ቆርሼ ከወጡ ጠቅሼ  የምሰጠው እርሱ ነው አላቸው ።ወዲያው እብስቱን ባርኮ አስራ ሶስት ፈትቶ እንካቹሁ ነገ በመልዕልተ መስቀል የሚዋው ስጋዬ ይህ ነው እንካችሁ ብሉ ብሎ ተቀብሎ አቀበላቸው ጽዋውንም አክብሮ ለውጦ ለብዙኃን ኃጢያአት የሚፈሰው የሐዲስ ስርዓት ደሜ ይህ ነው ። ጠጡ ብሎ ሰጣቸው ስጋውን ደሙን በመብል ያደረገው መብል መጠጥ ያፋቅራል እና ሰው እና እግዚአብሔርን የሚያፋቅር የሚያዋህድ መሆኑን ለማጠየቅ ነው  ደግሞስ በስንዴ እና በወይን ለምን  አደረገው ቢሉ ትንቢቱን እና ምሳሌውን ለመፈጻም ነው  መዝ4፥ 7 ሲራ 34፥26 ምሳለውም አምሳለሁ ለወልደ እግዚአብሔር የተባለ ካህኑ መልከጸዴቅ  በስዴ  በወይን ያሰታኩት ነበር እና ። ጌታም  ተቀብሎ  ማቀበሉ  ለአብነት ነው ይህውም  ካህናት ስጋውን ደሙን ለምህመናን ከማቀበላቸው  በፊት አስቀድመው እንዲቀበሉ  ምስሌ ሲተው ነው ።
               እንግዲእ ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርሰቶስ እንዲህ ባለ እውነተኛ ፍቅር ስጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ ህይወት የሆነን አምላከችን በመሆኑ ሁላችንም ለእርሱ  እንገዛለታለን ለአምላክነቱም ክብር እንሰግድለታለን ለክብሩም እንበረከካለን ።  አዞናል እና ስጋውን ደሙንም እንቀበላለን ዘወትርም  ቸርነቱን እያሰብን በእርሱ ምህረት ሰላማችንን እናረጋግጣለን በእርሱ ሞት እኛ ህይወትን አግኛተናል በትህትህናው ልህልናን ገንዘብ አድርጋናል ጠላታችን ተዋርዶልናል  ጽድቃችን ታውጆልናል እና ጌታ ሲሆን  የባሮቹን እግር ባጠበበት ቀን  ፍጽም ትህትናን እና ምሳሌነትን በግብር ስላስተማረን እኛም  ይህንን ቸርነት እና ፍቅር እየተመለከትን ባልጀሮቻችንን እንደራሳችን እየወደድን በንስሐ ታጥበን የርስቱ ወራሾች ያደርኝ ዘንድ  አምላካችን  ይርዳን 
                              ለብርሃነ ትንሳኤው በሰላም ያድርሰን ።

Saturday, April 16, 2011

ሆሳህና እምርት

ሆሣዕና (የዐቢይ ጾም 8ኛ ሳምንት)
የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ)
ወእንዘ ሰሙን በዓለ ፋሲካ ቀርቡ አርዳኢሁ ለአምላከ ጽድቅ ኀበ ደብረ ዘይት ሙራደ ዓቀብ ሀገረ እግዚአብሔር ወተቀበልዎ ሕዝብ ብዙኃን አዕሩግ ወሕፃናት ነሢኦሙ አዕፁቀ በቀልት እንዘ ይብሉ ሆሣዕና በአርያም ተፅዒኖ ዲበ ዕዋል ቦአ ሀገረ ኢየሩሳሌም በትፍሥሕት ወበሐሴት ይሁቦሙ ኃይለ ወሥልጣነ፡፡

ትርጉም: “በፋሲካ በዓል ሰሞን የእውነት አምላክ ደቀ መዛሙርት ወደ ደብረ ዘይት ቀረቡ፤ በሀገረ እግዚአብሔር (ኢየሩሳሌም) አቀበቱ ላይ ብዙ አረጋውያንና ሕፃናት የዘንባባ ቅጠል ይዘው ሆሣዕና በአርያም እያሉ ተቀበሉት፣ በአህያ ውርንጫ ላይ ተጭኖ በፍጹም ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ። ለእነዚህ ኃይልና ሥልጣንን ይሰጣቸዋል።
መልዕክታት
ዕብ.8÷1-ፍጻ. ከተናገርነውም ዋናው ነገር ይህ ነው፤ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፡፡ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፤ እርስዋም በሰው ሳይሆን በእግዚአብሔር የተተከለች ናት፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ)
 
1ኛ ጴጥ.1÷13 ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና ነቅታችሁ ኑሩ፤ ኢየሱስ ክርስቶስም ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ፡፡  (ተጨማሪ ያንብቡ)
ግብረ ሐዋርያት
የሐዋ.8÷26-ፍጻ. የእግዚአብሔር መልአክም ፊልጶስን ተናገረው፤ እንዲህም አለው÷ “በቀትር ጊዜ ተነሣና በደቡብ በኩል ከኢየሩሳሌም ወደ ጋዛ በሚያወርደው በምድረ በዳው መንገድ ሂድ፡፡” ተነሥቶም ሄደ፡፡” እሆም÷   (ተጨማሪ ያንብቡ)
ምስባክ
መዝ.80÷3 "ንፍሑ ቀርነ በዕለት ሠርቅ፡፡ በእምርት ዕለት በዓልነ፡፡ እስመ ሥርዓቱ ለእስራኤል ውእቱ"
ትርጉም፦ በመባቻ ቀን በታወቀችው በዓላችን ቀን መለከትን ንፉ፤ ለእስራኤል ሥርዐቱ ነውና÷ የያዕቆብም አምላክ ፍርድ ነውና፡፡
ወይም
መዝ.80÷2 "እምአፈ ደቂቅ ወሕፃናት አስተዳሎከ ስብሓተ፡፡ በእንተ ጸላዒ፡፡ ከመ ትንሥቶ ለጸላዒ ወለገፋዒ፡፡"
ትርጉም፦ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ፡፡ ስለ ጠላት÷ ጠላትንና ግፈኛን ታጠፋው ዘንድ፡፡
ወንጌል
ዮሐ.12÷1-11 ፋሲካ ከሚውልበት ከስድስተኛው ቀን አስቀድሞ ጌታችን ኢየሱስ ከሙታን ያስነሣው አልዓዛር ወደ ነበረበት ወደ ቢታንያ መጣ፡፡(ተጨማሪ ያንብቡ)
ቅዳሴ
ቅዳሴ ዘጎርጎርዮስ፡፡
መዝሙሩንና ምንባባቱን በዜማ ለማዳመጥ ይህን ይጫኑ

Friday, April 15, 2011

የመነኮሳት ሕይወት

የመነኮሳት ሕይወት

ምንም እንኳን የድንግልናና የምናኔ ኑሮ ቀደም ብሎ የተጀመረ ቢሆንም የምንኩስና መሥራችና አባት ቅዱስ እንጦንስ ነው፡፡ አባ እንጦንስ ግብፅ ውስጥ በምትገኝ ቆማ በምትባል ቦታ በ251 ዓ.ም ተወለደ፡፡ ወላጆቹ ሀብታሞችና ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ ከወላጆቹ ዕረፍት በኋላ የነበረውን ሀብት ለድሆች መጽውቶ መንኩሶ ብዙ ዓመት በብሕትውና ኖረ፡፡
በዚያን ጊዜ ብዙ ታምራትን ስለሠራ ሕዝቡ ግማሹ እሱን አይቶ ለማድነቅ የቀረው ደግሞ በእርሱ ጸሎት ለመፈወስ ወደነበረበት ቦታ ይጐርፍ ነበር፡፡ እርሱም በ356 ዓ.ም ዐረፈ፡፡

አባ ጳኩሚስ የተባለ ሌላው አባት በላይኛው ግብፅ ውስጥ ብዙ ገዳማትን በመሥራት የምንኩስናን ሕግና ሥርዓት በመወሰን ስለምንኩስና መስፋፋት ብዙ ደክሟል /290-347 ዓ.ም/፡፡ አንድ ቀን ወደ ዱር እንጨት ፍለጋ ሔዶ ሳለ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጸለትና እንደ አባቶቻችን ሐዋርያት የአንድነትን ማኅበር ለመሥራት መነኮሳትን እንዲሰበስብ አዘዘው፡፡ ብዙ አማኞች እየናፈቁት ማግኘት ያልቻሉትን ገዳማዊ ሕይወት ያገኙ ዘንድ ገዳም ለመመሥረት የሚስችለውንና የሚያስተዳድርበትን በነሐስ ላይ የተቀረጸ ሕግ ሰጠው፡፡ አባ ጳኩሚስም ከመልአኩ በተሰጠው ሕግ መሠረት የሚተዳደር ገዳም አቋቋመ፡፡ ይኸውም መነኮሳቱ ጠዋትና ማታ አብረው እንዲፀልዩ በአንድነት እንዲሠሩ ገቢና ወጪያቸው አንድ ላይ እንዲሆን በአንድነት እንዲመገቡ፣ ልብሳቸው አንድ አይነት እንዲሆንና እነዚህን የመሳሰሉትን ደንቦች አወጣላቸው፡፡ በዚህ መሠረት መነኮሳቱ የዕለት ምግባቸውን የሚያገኙት እየሠሩ ነበር፡፡ ከሴቶችም የምንኩስናን ሕይወት የጀመረች የአባ ጳኩሚስ እህት ማርያም ናት፡፡

ከዚህ በኋላ በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ጀምሮ ምንኩስና በግሪክ፣ በሮም፣ በሶሪያና በሌሎችም ሀገሮችም እየተስፋፋ ሄደ፡፡

የምንኩስናን ሕይወት ወደ ኢትዮጵያ ያመጡ በ5ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በጉባዔ ኬልቄዶን /በሃይማኖት ስደት/ ምክንያት ከቁስጥንጥንያ፣ ከግብፅ፣ ከሶርያ፣ ከሮም፣ ከአንጾኪያ ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ዘጠኙ ቅዱሳን መነኮሳት ናቸው፡፡ ምንኩስና ከተመሠረተ ጀምሮ በየጊዜው ሕዝቡ ታላላቆችም ሳይቀሩ ወደ ገዳማቱ እየሄዱ ይመነኩሱ ነበር፡፡
ነገር ግን ከ9ኛው መቶ ዘመን ጀምሮ በማኅበር ከሚኖሩት መነኮሳት መካከል ጥቂቶቹ ቀስ በቀስ ለብቻ በተለየ ቤት መኖር እያንዳንዱ መነኩሴ ለብቻ በፈለገበት ጊዜ መብላትና መተኛት ስለጀመረ በየገዳማቱ የመነኮሳቱ ኑሮ በማኅበር የሚኖሩትና ለብቻቸው የሚኖሩት ለሁለት ተከፈሉ፡፡

የድንግልና መሠረቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «ስለ መንግሥተ ሰማያት ሰውነታቸውን ጃንደረባ ያደረጉ አሉና፤ መፈጸም የሚችል ግን ይፈጽም» ሲል የተናገረው የሕግ ቃል ነው፡፡ ማቴ. 19፡12
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
/ምንጭ፦ 'የዛሬዋ ኢትዮጵያ በመጽሐፍ ቅዱስ' በዲ/ን አሐዱ አስረስ፣ ነሐሴ 1992 ዓ.ም/

ሁሉም በአግባቡና በሥርዐት ይሁን፡፡

                       ሁሉም በአግባቡና በሥርዐት ይሁን፡፡ /1ኛ ቆሮ.14፥40/

 
የአድዋ ድል መታሰቢያ ዕለት ነው፤ በጾም ወራት መንገድ ከመሔድም መጾም ይገባል ብዬ እኔ መንገደኛው ወደ መንፈሳዊ ጉባኤ ታደምሁ፡፡ ቀኑ ብሔራዊ በዓል በመሆኑ ሥራና ትምህርት ስለሌለ ጉባኤው በጊዜ እንዲጀመርና ብዙ ምእመናን እንዲታደሙ ምክንያት ሆኗል፡፡ ጉባኤው ከተጀመረ በመድረሴ የመጀመሪያው ትምህርት ወደ መጠናቀቁ ነበር፡፡ መርሐግብር መሪው ዐውደ ምሕረቱን እንደተረከቡና መዝሙር መዘመር እንደተጀመረ ግን ግራ የሚያጋባ ነገር ገጠመኝ፡፡
ዕልልታና ጭብጨባው ከዳር እስከዳር ያስተጋባ ጀመር፡፡ ግራ ገባኝ “ዐቢይ ጾም ገብቶ የለም እንዴ? …” አልኩኝ ለራሴ፡፡ አጠገቤ የነበረውን ሰው ቀስ ብዬ ጠየቅሁት “ምን ችግር አለው? ለእግዚአብሔር ክብር ነው!” አለና በእልህ የበለጠ ማጨብጨብ ጀመረ፡፡ በእጁ ጣውላ ይዞ የሚያጨበጭብ ይመስል ጭብጨባው በጣም ይጮኽ ነበር፡፡ በነገሩ ግራ መጋባቱን ያስተዋለው በቀኜ የተቀመጠ ጎልማሳ አንገቱን ወደ ጆሮዬ አስግጎ “ከሀገረ ስብከቱ እንዲጨበጨብና ዕልል እንዲባል ተፈቅዶአል!” አለኝ፡፡ ወዲያውም መርሐ ግብር መሪው “ምእመናን እርግጥ ነው ዐቢይ ጾም ቢሆንም ለእግዚአብሔር ክብር እልል በሉ፣ አጨብጭቡ፤ እስከ ሰሙነ ሕማማት ይቻላል!!” አያለ ማበረታቱን ቀጠለ፤ ከአንዳንድ አረጋዊያንና በሰል ካሉ ሰዎች በስተቀር ከታዘዝን ምን አስጨነቀን ያሉት ምእመናን “ፈቃድ የተሰጠውን እልልታና ጭብጨባ” አቀለጡት”፡፡

የእኔ ልብ ግን ጥያቄውን አላቁረጠም “ለእግዚአብሔር ክብር አጨብጭቡ የሚባለው ለምን ይሆን? አባቶቻችን በዐቢይ ጾም እልልታና ጭብጨባ እንዳይደረግ ሥርዓት የሠሩት ለእግዚአብሔር ንቀት ስለነበራቸው ነበር እንዴ? ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንስ ያለ አንዳች አሳማኝና አስገዳጅ ሁኔታ ሰው ደስ ይበለው ተብሎ በፈቃድ መጣስ ይቻላል እንዴ? ከቅዳሴ በላይ እግዚአብሔር የሚከብርበት ልዩ ሥርዓት የለም፡፡ ታዲያ ቅዳሴ ላይ የቱ ጋር ነው “እልልታና ጭብጨባ ያለው? “ ጥያቄው በዚህ የሚያቆም አይደለም “ለእግዚአብሔር ክብር በሚል ሥርዓት መሻር ከተቻለ “ለእግዚአብሔር ክብር ብለን የምንበላው ምግብ ውስጥስ ትንሽ ቅቤ ጣል ቢደረግበት..? ለእግዚአብሔር ክብር..?” በሺህ ለሚቆጠሩ ዓመታት የነበሩት አባቶቻችን በዐቢይ ጾም ሳያጨበጭቡ፣ ሳያሸበሽቡ የኖሩት የእኛን ያህል ለእግዚአብሔር ክብር መስጠት ሳያውቁ ነበር?፣ ወይስ በእነዚያ ዘመናት የነበሩት አበው ፈቃድ መስጠትን ሳያውቁበት ቀርተው ነው? መርሐ ግብር መሪው እንደነገረን “እስከ ሰሙነ ሕማማት ድረስ ለእግዚአብሔር ክብር የሚጨበጨብ” ከሆነ በሰሙነ ሕማማትስ ለምን ይከለከላል? በሰሙነ ሕማማት ለእግዚአብሔር ክብር አይሰጥም እንዴ?” ይህን ጥያቄ ውስጤ ከመጠየቅ አላርፍ አለኝ እንጂ እኔ እንኳን በተሰጠው ፍቃድ ተጠቅሜ እልል ለማለት ፈቃደኛ ነበርሁ፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ በዐቢይ ጾም ጭብጨባ መስማት ከተጀመረ ጥቂት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑም ግራ በመጋባት ፈራ ተባ እያለ ሲያጨበጭብ ከራርሞ ነበር፡፡ አሁን አሁን ግን ግራ መጋባት እየቀረ ማጨብጨብም እየተለመደ መጥቷል፡፡ ለብዙ ዓመታት የቆየን ክርስቲያናዊ ትውፊት እንደ ዋዛ ማፍረስ ቢቻልም በቀላሉ የማይመለስ /unrepairable/ መሆኑ ግን መታወቅ አለበት፡፡ ነገር ግን ያፈረሰው አካል ሁል ጊዜ የታሪክ ተወቃሽ መሆኑ አይቀርም፡፡

በጉባኤው የታደምኩበት ዕለት የዓድዋ ድል ቀን መሆኑን ብዙ ነገር አስታወሰኝ፡፡ የዐድዋ አርበኞች የጦር ሜዳ ውጊያ አርበኞች ብቻ ሳይሆኑ ለሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የመታመን አርበኞች ነበሩ፡፡ እንደ ሚታወቀው የዐድዋ ጦርነት የተካሔደው በዐቢይ ጾም ነበር፡፡ በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ወታደሮች ጾመው መዋጋት ስለሚከብዳቸው ሊቀ ጳጳሱ አቡነ ማቴዎስ እንዲፈቷቸውና ከጦርነቱ በኋላ እንዲጾሙ አጤ ምኒልክ ጠይቀው ነበር፡፡ ሊቀ ጳጳሱ ግን ይህንን ፈቃድ ለመስጠት እምቢ አሉ፡፡ /አንዳንድ ጸሐፍት ኢትዮጵያዊ ስላልሆኑ ነው ይላሉ/ በዚህ ጊዜ የቤተ ክርስቲያኒቱን ትእዛዝ ላለመተላለፍ ኢትዮጵያውያን እየጾሙ ተዋግተው ድል ነሡ፡፡ እንዲያው ለድምዳሜ ቸኮልክ አትበሉኝ እንጂ ለድሉ አንዱ ምክንያት ጾማቸው ነው ለማለት እገደዳለሁ፡፡ እነዚህ ወታደሮች ጾሙን ለማፍረስ አሳማኝ ሊባል የሚችል ምክንያት ማቅረብ ይችሉ ነበር፤ ግን አላደረጉትም፡፡ በየዘመናቱ በተከሰተው ድርቅ ጊዜም በዐቢይ ጾም ከብቶቻቸውን አርደው ላለመብላት ብለው ታምነው በረሃብ የሞቱትን ኢትዮጵያውያን፣ ተራብን ብለው የቤተ መቅደሱን የመገበሪያ ስንዴ ያልነኩ አባቶቻችን ጉዳይም ውል አለኝ፡፡ የልጅ ልጆቻቸው ግን “ለእግዚአብሔር ክብር እያልን ሥርዓት እንጥሳለን!” ምን አገናኘው እነርሱ የጾሙት ከምግብ የሚል ይኖራል፡፡ ሆድ ከምግብ ሲጾም እጅ ከጭብጨባ፣ አንደበት ከእልልታ መከልከሉስ አብሮ የተሠራ ሥርዓት አልነበረም?

እግዚአብሔር ካልጮኹ የማይሰማ፣ ካላደመቁ የማያይ አምላክ አይደለም፡፡ ከመላእክት ወገን እንኳን በአርምሞ /በዝምታ/ የሚያመሰግኑት አሉ፡፡ የእኛም ነፍስ ለማመስገን የግድ አንደበትና እጅ እንዲያግዟት አትሻም፡፡ ከኦሪት መጽሐፍ አንድ ታሪክ እናንሣ ሙሴ ሕዝበ እስራኤልን ይዞ ከባሕረ ኤርትራ ሲደርስ ከኋላ የፈርኦን ሠራዊት መጣባቸው፡፡ ሕዝቡ ሙሴ ላይ ጮኸበት፡፡ ነቢዩ ግን “እግዚአብሔር ዛሬ የሚያደርጋትን ማዳን እዩ!” ብሎ ሕዝቡን አረጋጋ፡፡ በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር ሙሴን፡- “ለምን ትጮኽብኛለህ” አለው፡፡ የሚያስደንቀው ነገር ሙሴ እንኳን እርሱ ሊጮኽ የሚጮኹትንም ሰዎች ያረጋጋው እርሱ ነበር፡፡ እግዚአብሔርን ለምን ትጮኽብኛለህ ያሰኘው የሙሴ የልቡ ጩኸት ነበር፡፡ እግዚአብሔር ያለ ጩኸት ያለ እልልታ ያለ ጭብጨባ የሚሰማ አምላክ ነው፡፡ መናገር የተሳናቸውን ሰዎችም ጸሎት ከሁሉ ይልቅ ያዳምጣል፡፡ ለዚህ ነው ቤተ ክርስቲያን በታላቁ ጾም በእርጋታና በጸጥታ ከፈጣሪ እንድንገናኝ ሥርዓት የሠራችው፡፡ ወቅቱም ራስን በእርጋታ የመመልከቻ፣ የጽማዌ፣ የተዘክሮ /meditation/ ጊዜ እንጂ የግርግርታ ጊዜ አይደለም፡፡ ስለ ጌታችን ጭምትነት የተጻፈው “አይጮኽም አይከራከርም፤ በአደባባይ ድምጹን የሚሰማ የለም፤ የተቀጠቀጠ ሸንበቆን አይሰብርም፤ የሚጤስ የጥዋፍን ክርም አያጠፋም” ተብሎ ነው፤ በገዳመ ቆሮንቶስም በእርጋታና በጸሎት እንጂ በጩኸት እንደቆየ አልተጻፈም፡፡ በዓመት ለሁለት ወራት ብቻ እንኳን መረጋጋት የከበደው ሰው መንፈሳዊነቱ ምኑ ላይ ነው?
 /ምንጭ፦ሐመር ፣18ኛ ዓመት፣ ቁጥር 12 ፣ መጋቢት 2003ዓ.ም/